አዎ! ኦነግ ነኝ! ኦሮሞን ነጻነት ለማውጣት ግንባር የፈጠርኩኝ የኦሮሞ ልጅ ነኝ::

January 12, 2014  | Gadaa.com | ከከተማ ቦሬሳ*

ኢትዮጵያ ውስጥ የሕዥቦች መብት ተከብሮ አያውቅም:: በየግዜው የሚነሱ መሪዎች የሕዥቦች መብት አክብረው ሳይሆን ረግጠውና አፍነው መኖርን ነው የሚመርጡት:: የታፈነ ህዝብ፣ የተጨቆነ ህዝብ ሁሌም ለሰላም ይዘምራል፤ ሁሌም ሰላምን ለማምጣት ይታገላል:: እናም የኦሮሞ ህዝብ ትግል ከዚህ የመነጨ ነው ጥያቀውም አንድና ግልጽ ነው – ነጻነት!
ነጻነት! ይህ የመላው የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ነው:: አዎ! ነጻነት፤ ነጻ አእምሮ የሌለው ነጻ አስተሳሰብ የለውም:: የኢትዮጵያ ገዚዎች ነጻ አስተሳሰብ የላቸውም በነጻነት አያምኑም፤ ኦሮሞን በነጻነቱ እንዲኖር ከመፈቀድ ይልቅ ለፖለቲካቸው መጠቀሚያ በማድረግ ጭቆናና ግፍ፣ እስራትና ሞት ከእለት ወደ እለት እየባሰና እየከፋ መጥቶአል:: የኦሮሞ ህዝብ ሰለ ነጻነቱ መታገል ከጀመረ ብዙ አመታት ሆኖታል:: ዛሬም በትግል ላይ ነው:: የምንፈልገው ነጻነት እስኪመጣ ድረስ እንታገላለን::

ትግል! የኦሮሞ ህዝብ ሰራተኛ ነው:: የኦሮሞ ህዝብ የተማረ ነው:: የኦሮሞ ህዝብ ሰው አክባሪ ነው:: የኦሮሞ ህዝብ አገሩን ለማሳደግ የሚደክም ህዝብ ነው:: የኦሮሞ ህዝብ በወደደና ባፈቀረ፣ በተማረና ባስተማረ፣ ስራ በሰራና አገር ባሳደገ – ይህ ሁሉ በደልና ግፍ ለምን?!
ተዉ! ህዝባችንን አትበድሉ አትጨቁኑ ብሎ መተየቅ … ኦነግ ነህ ተብሎ ያሳስራል::
ተዉ! ተማሪዎቻችንን ከትምህርት ገበታቸው ላይ አታባሩ ብሎ መጠየቅ … ኦነግ ነህ ተብሎ ያሳስራል::
ተዉ! መምህሮቻችንን በነጻነት እንዲያስተምሩን ይሁን ብሎ መጠየቅ … አንተ ኦነግ ነህ ተብሎ ያሳስራል::
ተዉ! ገበሬዎቻችንን ከመሬታቸው አታፈናቅሉ ብሎ መጠየቅ … ኦነግ ነህ ተብሎ ወደ እስር ቤት ያስገባል::
ሰራተኞች እና አርቲስቶች ከኦነግ ጋር ግኑኙነት አላችሁ ተብለው ለስራ እንደወጡ አልያም ከቤታቸው ታፍነው የተገደሉ እና የታሰሩ መጠየቅ … አንተ ኦነግ ነህ ተብሎ ያሳስራል::
አላወቁም እንጂ ሁሉም የኦሮሞ ህዝብ ነጻነቱን ፈላጊ ነው:: የኔም መልስ – አዎ! ኦነግ ነኝ!
አዎ! ኦነግ ነኝ! የኦሮሞን ነጻነት የምናፍቅ በነጻነት መኖርን የምመኝ ስለ ነጻነት የምታገል፤
አዎ! ኦነግ ነኝ! ገበሬው ከመሬቱ ሲፈናቀል የሚያመኝ መብቱ ሲረገጥ የማልወድ፤
አዎ! ኦነግ ነኝ! ተማሪው ተምሮ ወገኑን ይረዳል አገር ይረከባል ሲባል በጭቆናና በበደል በግፍ ከትምህርት ገበታው ሲባረር፤
አዎ! ኦነግ ነኝ! አስተማሪው የነገ አገር ተረካቢ ለማፍራት ሲጥር ሲደክም በኦሮሞነቱ ብቻ ከመምህርነቱ ሲነሳ ሲባረር!
አዎ! ኦነግ ነኝ! ሰራተኛው ኦሮሞ ስለሆነ ብቻ ለኦሮሞ ነጻነት ግንባር ትረዳለህ ተብሎ ከስራው ቦታ ታፍኖ ተወሰዶ ሲገደል፣ ሲታሰርና ሲባረር፤
አዎ! ኦነግ ነኝ! አርቲስቱ ሲያቀነቅን፣ ሲያዜም ይሄ ለቅስቀሳ ነው፣ ፖለቲካዊ አጀንዳ አለው ተብሎ ሲታሰሩ ከአገር ሲሰደዱ፤
አዎ! ኦነግ ነኝ! ኦሮሞን ነጻነት ለማውጣት ግንባር የፈጠርኩኝ የኦሮሞ ልጅ ነኝ::
============================================================
ከተማ ቦሬሳ: waqjirak@yahoo.com

No comments:

Post a Comment