የመለስ ዜናዊ አስከሬን በቦሌ የሬሳ ማቀዝቀዣ ክፍል ውስጥ ተቀምጧል!!


August 21/2012 (ኢ.ኤም.ኤፍ) የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊ ከዚህ አለም መለየታቸው የ”አዋጁን በጆሮ” ዜና ኦገስት 21፣ 2012 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ገልጿል። ከጥቂት ቀናት በፊት የአቶ መለስ ዜናዊ አስከሬን፤ ከውጭ አገር በግል አውሮፕላን እንዲገባ ተደርጎ በቦሌ ተርሚናል የሬሳ ማቀዝቀዣ ክፍል ውስጥ ተቀምጦ ነበር የቆየው። ሆኖም በኢቲቪ የዜና እወጃ ላይ፤ “በትላንቱ ምሽት በድንገት ህይወታቸው አልፏል።” የሚል ውሸት በድጋሚ ተሰምቷል። የአቶ መለስ ዜናዊ አስከሬን ወደ ሬሳ ማቀዝቀዣ ክፍል ከመግባቱ በፊት፤ በዚያ የነበሩ ሌሎች አስከሬኖች በሙሉ እንዲወጡ አስቸኳይ ትዕዛዝ ተሰጥቶ ነበር። ከዚያም አስከሬኑ በግል አውሮፕላን መጥቶ በከፍተኛ ጥበቃ ወደ ሬሳ ማቀዛቀዣ ክፍል ከተወሰደ በኋላ እስካሁን ድረስ በወታደር እየተጠበቀ ነው የሚገኘው። ሆኖም አስከሬኑን ወደሌላ ሆስፒታል፤ ቢያንስ ጦር ኃይሎች ሆስፒታል አለመውሰዳቸው የሰዎቹን አለመረጋጋትና ፍራቻ የሚያሳይ ምልክት ነው። የአስከሬኑ በቦሌ ተርሚናል የሬሳ ማቀዝቀዣ ክፍል የመቆየቱ ሁኔታ እስከቀብሩ ስነ ስር ዓት ድረስ የሚቆይ ይመስላል። የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር አስከሬን በቦሌ የሬሳ ማስቀመጫ ክፍል ውስጥ በመቀመጡ ምክንያት ሌሎች ከውጭ የሚገቡ ኢትዮጵያውያን አስከሬን ወደ በረዶ ቤት ሳይገባ በቀጥታ ቤተሰቦቻቸው እንዲረከቡ እየተደረገ መሆኑን ለማወቅ ችለናል።

ከላይ የገለጽነውን ዜና አዘጋጅተን፤ አስከሬኑ ለቀናት በቦሌ ተርሚናል በረዶ ክፍል ውስጥ መቀመጡን ተችተን ዜናውን ለማውጣት በዝግጅት ላይ ሳለን ነው የአቶ መለስ ዜናዊ በድንገት ሞቱ ሲል ኢቲቪ የዋሽው። አስተያየት ሰጪዎች፤ “ሰውየው ሞተው ቋንጣ ሊሆኑ ነው” እያሉ ባለበት ወቅት ነው ኢቲቪ “ትላንት ማታ በንገት ሞቱ” ብሎ ፈገግ ያሰኘን።
በሌላ በኩል ለረዥም ጊዜያት እውነቱን ሲክድ የነበረው በረከት ስምኦን… “መለስ በቅርቡ ወደ ስራ ይመለሳሉ” በማለት፤ የሃሰት ቃል ሲያቀብል ከቆየ በኋላ ዛሬ ማለዳ ላይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊን መሞት ለማርዳት በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ለማለት እንኳን ሳይደፍር ቀርቷል። (ሆኖም ዜናው በቴሌቭዥን ከተነገረ ሁለት ሰዓታት በኋላ አቶ በረከት በተረበሸ እና ባልተረጋጋ ሁኔታ መግለጫ ሰጥቷል። በመግለጫው መጀመሪያ ላይ መለስ ዜናዊን በማሞገስ፤ ከዚያም አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ጠቅላይ ሚንስትርነቱን ሸፍኖ እንደሚሰራ፣ አቶ ኃይለማርያም ደርቦ ይሰራ የነበረውን ውጭ ጉዳይ ሚንስትርነት ሌላ ሚንስትር ተክቶ እንደሚሰራ እና የቀብር ስነ ስር አቱን ለማስፈጸም የተቋቋመ ኮሚቴ መኖሩን ገልጿል።) የአቶ መለስ ዜናዊ ዜና እረፍት ከተሰማ በኋላ፤ ልጆቻቸውን በመለስ አስተዳደር የተነጠቁ ወላጆች፤ ፍትህ አጥተው በእስር እና በስደት ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ደስታቸውን ሲገልጹ፤ ቀኑ የጨለመባቸው የኢህአዴግ ወገኖች ደግሞ ሆድ ብሷቸው ሲያለቅሱ ውለዋል።

የመለስ ዜናዊ አስከሬን በቦሌ የሬሳ ማቀዝቀዣ ክፍል ውስጥ ተቀምጧል!!
በአሁኑ ወቅት. የመለስ ዜናዊን ቦታ ተክተው እንዲሰሩ የተደረጉት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ሲሆኑ፤ ቀደም ሲል ደርበው ይሰሩት የነበረውን የውጭ ጉዳይ ሚንስትርነት ቦታ የህወሃት አባል የሆኑት አቶ ብርሃነ ገብረክርስቶስ ሸፍነው እየሰሩት ይገኛሉ። የጠቅላይ ሚንስትርነቱ ቦታ ወደ ሌላ ብሄር መሄዱ በዘረኝነት አጥር ውስጥ የሚገኙትን በተለይም፤ የህወሃት ከፍተኛ አመራር እና የጦር አዛዦችን ያስኮረፈ ይመስላል። በአሁኑ ወቅት ጄነራል የሳሞራ የኑስን ህመም ተከትሎ የኢትዮጵያ የጦር ሰራዊት በአስጨናቂ መንታ መንገድ ላይ ይገኛል። የአየር ኃይል እና የምድር ጦር ሰራዊት ከአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መስመር ውጪ፤ በህወሃት ከፍተኛ የጦር መኮንኖችም አመራር ስር ስለወደቀ አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር በነዚህ ጄነራሎች ላይ የማዘዝ ስልጣናቸው ውሱን እንደሆነ ግምት እየተሰጠ ነው።
የአባ ጳውሎስ የቀብር ስነ ስር ዓት የፊታችን ሃሙስ በቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የሚከናወን ሲሆን፤ የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር የቀብር ስነ ስር ዓት የት እና መቼ እንደሚከናወን አልታወቀም። ሁለቱም ሰዎች በጥቂት ቀናት ልዩነት መሞታቸውን የታዘቡ ሰዎችም፤ ክስተቱን “ፍቅር እስከ መቃብር።” ብለውታል።
ዛሬ በታወጀው የኢቲቪ ዜና ላይ መለስ ዜናዊ ትላንትና በድንገት ሞቱ ይበል እንጂ፤ የት እንደሞቱ አልገለጸም። እውነቱ ግን አሁንም የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ አስከሬን፤ ከውጭ አገር ከገባ በኋላ በቦሌ ተርሚናል የሬሳ ማስቀመጫ ክፍል ውስጥ ይገኛል። አስከሬኑ ወደ ሆስፒታል አለመሄዱና ለቀናት ያህል በቦሌ ሬሳ ቤት መቀመጡ ለመለስ ዜናዊ ክብር ሳይሆን ውርደት ነው። በቦሌ በረዶ ቤት ስለተቀመጠው አስከሬን… አቶ በረከት ስምኦን ምን እንደሚሉን አናውቅም። በአሁኑ ወቅት የጦር ኃይሉ በአንደኛ ደረጃ ተጠንቀቅ ላይ እንዳለ ሆኖ፤ የጦር አዛዡን የጄነራል ሳሞራ የኑስን የሞት ወይም የመሰንበት ዜና እየተጠባበቀ ነው።

1 comment:

  1. http://www.diretube.com/latest/the-body-of-pm-meles-zenawi-arrived-at-his-office-video_dcbcc62be.html
    ዛሬ የመለስ ዜናዊ ሬሳ ወደ ጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት መድረሱ ተዘገበ

    ReplyDelete