አሜሪካ የተደበቀው ወንጀለኛ

ኢየሩሳሌም አርአያ
September 09/2012

የህወሃት አባል ነው ። ከትጥቅ ትግሉ ዘመን አንስቶ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር ስልጣን እስከተቆናጠጠበት ጊዜ ድረስ ያለው የጀርባ ታሪክ በንጹሃን ደም የተጨማለቀ እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ። ይህ ግለሰብ ተስፋዬ መረሳ ይባላል። ህወሃት ጫካ በነበረበት ጊዜ ተራው ታጋይ ከሴት ጋር የፍቅርም ሆነ የግብረ ስጋ ግኑኝነት ማድረግ እንደማይፈቀድለት አስገራሚው የፓርቲው ህግ ይደነግጋል። ይህ ህግ እስከ 1981 አ.ም የቆየ ሲሆን የበላይ አመራሩ ግን የፈለገውን የማድረግ መብት ነበረው። ፆታዊ ግንኙነት ሲያደርጉ የተገኙ ተራ ታጋዮች ይፈፀምባቸው የነበረው ቅጣት በጥይት ተደብድቦ መገደል ነበር። በሺህ የሚቆጠሩ የፓርቲው ተራ አባላት የዚህ ቅጣት ሰለባ ሆነዋል። እነዚህ ታጋዮች እንዲረሸኑ ሲወሰን ለመግደል ይጣደፉ ከነበሩት እና በርካታው የፓርቲ አባላት ከሚያስታዉሷቸው ገዳዮች አንዱ እና ቀንደኛው ተስፋዬ መረሳ ሲሆን ፣ ከእርሱ በተጨማሪ ኢሳያስ ወ/ጊዮርጊስ፣ ወ/ስላሴ ፣ሃይሉ (ሳንቲም) … በጭካኔ የግድያ ተግባራቸው ይጠቀሳሉ። ፊደል ያልቆጠሩት እነዚህ ወንጀለኞች የገዛ የትግል ጓዶቻቸውን ለመረሸን እጅ በማውጣት “እኔ… እኔ” እየተባባሉ ያሳዩ የነበረው ሰይጣናዊ ፉክክር እና ጥድፊያ ብዙ የፓርቲው አባላት አሁን ድረስ ያስታውሱታል።

አቶ መለስ እነዚህን ግለሰቦች በደህንነትና ፖሊስ ቁልፍ ቦታ ያስቀመጡአቸው የታዘዙትን እንደሚፈጽሙላቸው ጠንቅቀው ስለሚያውቁ ነበር ። እነ ተስፋዬ “ግደሉ “ሲባሉ “ስንት?” ነበር የሚሉት ።በገሃድም የታየው ይሄው ነበር ።

የክልል 14 ፖሊስ ኮሚሽነር የነበሩት እና በህግ ዲግሪ የነበራቸው ሻለቃ በፍቃዱ ቶሌራ በ1996 አ.ም ያለ አንዳች ጥፋት እንዲነሱ ተደርጎ ፣በምትካቸው ወደ ስልጣን እንዲመጣ የተደረገው ተስፋዬ መረሳ በምርጫ 97 የአቶ መለስን ትእዛዝን በመቀበል የበርካታ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ደም እንዲፈስ አድርጓል ።በመቶዎች የሚቆጠሩ አካላቸው እንዲጎድል ፣በሺዎች የሚቆጠሩ እስር ቤት እንዲጋዙ ፣በርካቶች ከስራቸው እንዲባረሩ አድርጓል።ከአዲስ አበባ ፖሊስ 400 የሚጠጉ አባላትን በቅንጅት ደጋፊነት እና አባልነት በመፈረጅ እንዲባረሩ ወስኖአል።

በወቅቱ ለዚህ የወንጀል ተግባሩ ከአቶ መለስ ሙገሳ እና ውዳሴ ለማግኘት በቅቶአል። አስገራሚው ነገር ይህ ወንጀለኛ በዚህ የጭካኔ ተግባሩ የልብ ልብ ተሰምቶት ሸራተን ጎራ ማለት ይጀምራል። የተስፋዬ ሸራተን መጥቶ መለኪያ ማንሳት ያላስደሰታቸው ሽማግሌው ስብሃት ነጋ «አቅሙን፣ደረጃውን፣ልኩን አይቶ አይጠጣም?እዚህ መጥቶ ከእኛ እኩል መጠጣት እና መዝናናት ይፈልጋል ?የምን መዳፈር ነው ?» ሲሉ ንዴት የተሞላበት ተግሳፅ እንዲደርሰው ያደርጋሉ ።የስብሃት አደገኛነት የት እንደሚደርስ እና ምን አይነት የበቀል መዘዝ እንደሚያስከትል ጠንቅቆ የሚያውቀው ተስፋዬ አሳቻ ጊዜ ሲጠብቅ ይቆያል።

በ2000 አ.ም ከቢጤዎቹ ጋር አንድ ፕላን ይነድፋል። ከደህንነት ሹሞች ከነኢሳያስ ጋር የመከረው ጉዳይ ጥንቃቄ በተሞላበት መልኩ ተፈጻሚ ለማድረግ ተንቀሳቀሱ ።የምክክሩ ምስጢር ይህ ነበር ። በአዲስ አበባ በተለይ ፒያሳ፣አራት ኪሎ ፣ከጊዮን_- ፍልዉሃ እስከ ኢትዮጵያ ሆቴል ጀርባ ፣አሜሪካ ግቢ፣ መርካቶ ፣ቦሌ፣22 ማዞሪያ፣መገናኛ እና በመሳሰሉት አካባቢዎች ከፍተኛ የዶላር ጥቁር ገበያ ይካሄዳል። ከጠዋቱ 4፡00 ሰአት ሲቪል የለበሡ በሺህ የሚቆጠሩ የደህንነት አባሎች በሁሉም መደብሮች በር ላይ በተመሳሳይ ሰአት እንዲገኙ ከተደረገ በኋላ በዚያው ቅጽበት ከተስፋዬ “ጀምሩ”የሚል ትእዛዝ ሲተላለፍ… መሳሪያ እየደቀኑ ዶላሩን ጠራርገው ከየመደብሩ በሃይል ወሰዱ ። ከአሜሪካ ግቢ ብቻ ከስምንት መቶ ሺህ ዶላር በላይ ሲገኝ በአጠቃላይ 4.5ሚልዮን ዶላር ገደማ በጉልበት ተወረሰ ። ከዶላር በተጨማሪ ከመርካቶ እና ፒያሳ ከ2 ሚሊዮን የበለጠ ጥሬ ገንዘብ(የኢትዮጵያ ብር) ተወስዶአል። በ1984-85 አ.ም በወቅቱ የሃገሪቱ ፕረዚዳንት የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ የዶላር ጥቁር ገበያን አስመልክተው ሲናገሩ “ምንዛሬውን ከወቅቱ ገበያ ጋር እኩል እናካሂደዋለን እንጂ የጥቁር ገበያውን ቁጥጥር አናደርግበትም ፣አንነካውም “በማለት ተናግረው እንደነበር ብዙዎች ያስታውሱታል። ሆኖም ግን በቃሉ የማይገኘው የኢህአዴግ መንግስት በጠራራ ፀሃይ የለየለት የአደባባይ ዝርፊያ ሲያከናውን በርካቶች ኑሮአቸው ተናግቶአል፤ አንዳንዶችም ህይወታቸውን እስከማጥፋት ደርሰዋል።

ይህ ገንዘብ በቀጥታ ገቢ የተደረገው ወይም የተረከበው ተስፋዬ መረሳ ነበር ።በወቅቱ በመንግስት ሚዲያ ህገወጥ የዶላር አዘዋዋሪዎች እጅ ከፍንጅ እንደተያዙ እና ገንዘቡ ለመንግስት ገቢ መደረጉን የገለጸው ተስፋዬ፣ይህንን በተናገረ በሳምንት ልዩነት የተዘረፈውን ገንዘብ በሳምሶናይት ይዞ በቦሌ ወደ ኬንያ አመራ ።ከዚያም ወደ አሜሪካን አቀና ።ይህ በንጹሃን ደም የታጠበ ወንጀለኛ እና ዘራፊ አሜሪካን እንደመሸገ የተረጋገጠ ቢሆንም፣የት ከተማ እንዳለ እና እንደሚኖር ማወቅ አልተቻለም።

No comments:

Post a Comment