ኦህዴድ ዉስጥ የተፈጠረዉ ክፍፍልና ልዩነት ስር እየሰደደ ነው

[ግንቦት 7 ዜና]:

ወያኔ ኢትዮጵያን እንዳሻዉ መግዛት እንድችል በአምሳሉ ከፈጠራቸዉ ሦስት ድርጅቶች አንዱ በሆነዉ በኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) ዉስጥ በቅርቡ የተካሄደዉን ከፍተኛ የስልጣን ክፍፍል አስመልክቶ የተፈጠረዉ ልዩነት ከፓርቲና ከክልል አልፎ ዞን ደረጃ ላይ የወረደ መሆኑን የግንቦት ሰባት ድምጽ ዘጋቢ የኦህዴድ የሚገኙ ዉስጥአዋቂ ምንጮችን ጠቅሶ በላከልን ዜና ገለጸ። ዘጋቢያችን ያናገራቸዉና ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ ከፍተኛ የኦህዴድ አመራር አባል እንደተናገሩት በድርጅታቸዉ ዉስጥ የተፈጠረዉ መከፋፈል ከላይ ወደታች ወርዶ ኦህዴድ ዉስጥ ሁለት ቡድኖች መፈጠራቸዉን ሳይደብቁ ተናግርዋል። ከተፈጠሩት ሁለት ቡድኖች አንደኛዉ አሁን በስልጣን ላይ የሚገኘዉን የሀይለማሪያም ደሳለኝን መንግስት ተቀብለን እንሂድ የሚል ሲሆን ሁለተኛዉ ቡድን ደግሞ የኦሮሞን ህዝብ ብዛትና ኦህዴድ በኢትዮጵያ ፓርላማ ዉስጥ ያለዉን መቀመጫ ብዛት ከግምት ዉስጥ ባላስገባ መልኩ የተመሰረተዉን የሀይለማሪያም ደሳለኝን መንግስት በፍጹም መቀበል የለብንም ባይ ነዉ።

“ብዙሃኑ በአናሳ አይገዙም” የሚል መፈክር አንግቦ የተነሳዉ ይህ ቡድን ብዙዉን የኢትዮጵያ ህዝብ ለሚወክለዉ ለኦህዴድ የጠ/ሚኒስትርነቱም ሆነ የምክትል ጠ/ሚኒስትርነቱ ቦታ አለመሰጠቱ የሚያመለክተዉ ኦህዴድን በመሳሪያነት ለመጠቀም የሚደረገዉን ጥረት ነዉና በፍጹም አንቀበለዉም ብሏል። በኦህዴድ ዉስጥ የተፈጠረዉ ክፍፍል ስር ሰድዶ የሚታየዉ በሀረሪ ክልል ሲሆን ከዚህ በፊት ተነስቶ ያወዛገበዉ “ክልሉን ማን ያስተዳድረዉ” የሚለዉ ጥያቄ አንደገና ማገርሸቱ ታዉቋል።

በኦህዴድ ዉስጥ የተፈጠረዉ ልዩነት በዚህ ከቀጠለ ኦህዴድ በዋናዉ ግንባር በኢህአዴግ ዉስጥ በሚጫወተዉ ሚና ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ እንደሚያደርግ የሚታወቅ ሲሆን ኦህዴድ በኢህአዴግ ዉስጥ የሚጫወተዉ ሚና የኦሮሞን ህዝብ ብዛት የማይመጥን ከሆነ የኦህዴድም ሆነ የኢህአዴግ የወደፊት እድል ከፈተኛ አደጋ ላይ ሊወድቅ እንደሚችል ብዙ የፖለቲካ ተንታኞች በመናገር ላይ ናቸዉ። ከዚህ በተጨማሪ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር  ሀይለማሪያም ደሳለኝ የኦህዴድን ሙሉ ድጋፍ ሳያገኝ ምን ያክል ስራ መስራት እንደሚችል ብቻ ሳይሆን ለምን ያክል ግዜ በስልጣን ላይ መቆየት እንደሚችል አጠያያቂ እየሆነ መጥቷል። ይህ በእንዲህ እንዳለ  ሀይለማሪያም ደሳለኝ ስልጣን ከያዘ የሰነበተ ቢሆንም እስካሁን ድረስ የራሱን ካቢኔ መመስረት ያልቻለዉ በኦህዴድና በህወሀት ዉስጥ በተፈጠረፈዉ የርስበርስ ልዩነትና ቅሬታ  የተነሳ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።

Abbay Media  

No comments:

Post a Comment