በዲያስፖራ ያለውን የወቅቱን የኢትዮጵያ ፖለቲካ በማስመልከት በአውሮፓ የኦሮሞ ወጣቶችና የሴቶች ማህበራት የጋራ መግለጫ: እኛም በመጀመሪያ ደረጃ ኦሮሞ ነን።

July 24, 2013

በአሁኑ ወቅት የኦሮሞ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ እድገት እርር ድብን ያደረጋቸው የአጼዎቹ ቡችሎች በአጼዎቹ ልጆች በተፈጠሩ ሚዲያዎች ላይ አንድን ግለሰብ በማስታከክ በኦሮሞ ህዝብ ላይ የቃጡትን ሀሰታዊ የፖለቲካ ዘመቻ ለህመማቸው ፈውስ ሳይሆን ማባባሻ እንደሆነ ልናስጠነቅቃቸው እንወዳለን።

ነጻነት ዲሞክራሲና እኩልነት ስራ ላይ በሚውልበት ሀገር ውስጥ እየኖሩ ስለነጻነት ዲሞክራሲና እኩልነት የማይረዱ ግለሰቦች በምን አይነት መልኩ ሊማሩ እንደሚችሉ መገመት አዳጋች ነው። ለማመን በጣም አስቸጋሪ የሚሆነው ደግሞ እነዚህ ግለሰቦች በትምህርት ደረጃ ማእረጋቸውና በአስተሳሰባቸው መሀከል ያለው ርቀት የሰማይና የመሬት ያህል መሆኑ ነው።


ለመሆኑ ማነው እነሱን የኢትዮጵያ ባለቤትና የኢትዮጵያዊነት ትርጉም ፈቺ ያደረጋቸው? የፈለጉትን ንፁሕ ኢትዮጵያዊ: የፈለጉትን ጠንካራ ኢትዮጵያዊ: እንዲሁም ባንዳ ወይም ከሃዲ እያሉ የሚጠሩበትን መስፈርት ማነው የሰጣቸው? የአጼዎቹ አሊያም የአምባገነኑ የደርግ ስርአት መስፈርት መሆኑ ነው?
አክራሪ ወይም ሽብርተኛ የሚለውስ ከመለስ ዜናዊ ተኮርጆ ነው?
ከሁሉ አስቀድመን እነሱ በሚረዱት የሳባ ፊደል ሀ ብለን ልናስተምራቸው የምንወዳቸው ነጥቦች:
1ኛ፡ አሁን ኢትዮጵያ ተብላ የምትጠራው ኢምፓየር የአጼዎቹ ንብረት ሳትሆን አጼዎቹ በጉልበት የፈጠሯት እንደሆነች፡ ያም ማለት የኢትዮጵያ ወራሾች የአጼዎቹ አመልኪዎች ብቻ ሳይሆኑ የአጼዎቹ ሰለባዎችም መሆናቸውን፡
2ኛ፡ ኢትዮጵያዊነት ነህ፡ነሽ ተብሎ የሚሰጥ ዜግነት ሳይሆን ህዝቦች በፈቃዳቸው ወደው የሚቀበሉት የማንነት መገለጫ መሆን እንዳለበት፡ ያንን ለማምጣት ደግሞ ለምን ቅድሚያ ኦሮሞ ነኝ አልክ እያሉ የጥላቻና የሀሰት ዘመቻ በጀዋር ወይም በሌሎች ኦሮሞዎች ላይ በመክፈት ሳይሆን ውይይቶችን በማካሄድና ነጻ የሃሳብ መድረኮችን በመፍጠር እንደሆነ::
እኛ በአውሮፓ የኦሮሞ ወጣቶችና የሴቶች ማህበራት በአሁኑ ወቅት በአልጀዚራ ላይ ቅድሚያ ኦሮሞ ነኝ በማለቱ ብቻ በፖለቲካ ምሁሩ ጀዋር ላይ የተከፈተውን የሀሰት ዘመቻ ማውገዝ ብቻ ሳይሆን ለመከላከልም በመገደዳችን ይህ አይነቱ አጼያዊ ዘመቻ እስኪያቆም ድረስ ከቅርብ ጊዜ በፊት ከሰላም ወዳድ የአንድነት ሀይሎች ጋር የጀመርነውን የቅርርብ ዲያሎጎችና የሀሳብ ልውውጦች በይበልጥ ልንገመግምው ወስነናል። ምክኒያቱም አንዳንድ ጉዳዩን ሊረዱ የማይችሉ ወይም ሊረዱ የማይፈልጉ ግለሰቦች የኛን የቅን አካሄድ እጅ እንደመስጠት አድርገው ሲሰብኩና የኦሮሞ ህዝብ ትግልንም ውጤት አልባና ውድቅ አድርገውም ሊጽፉ ሲሞክሩ ይታያሉ።

በአጼዎቹና በአምባገነኑ ዘመን የነበረውን የኦሮሞ ህዝብ ፖለቲካዊና ማህበራዊ መልክና ይዘት ከአሁኑ ጋር ሲነጻጸር ያለውን ለውጥ በፊልም ካላሳየናቸው በቀር እንደማይገባቸው አሁን አሁን ተረድተናል።
ከ 15 እስከ 25 ሚሊዮን የሚጠጋው በቋንቋው እየተማረ ያለው የኦሮሞ ልጅ በማን የትግል ውጤት እንደሆነ ምናልባት በእግዚአብሄር መልዕክተኛ ካልተነገራቸው በቀር ሰው የሚነግራቸውንም ሆነ በአይናቸው የሚያዩትን ማመን ተስኗቸዋል።
ያም ሆነ ይህ እነዚህን ትምክህተኞች በወንድማችን ጀዋር ላይ እያደረጉ ያሉትን አጼያዊ ዘመቻ ለራሳቸው ህልውና ሲሉ እንዲያቆሙ እያስጠነቀቅናቸው፡
1ኛ፡ ሌሎች በዲያስፖራና በሀገር ቤት የሚገኙ የነጻነት: የዲሞክራሲና የእኩልነት መብት ታጋዮች ሁሉ ይህንን አጼያዊ ዘመቻ እንዲያወግዙ እንጠይቃለን።
2ኛ፡ በዲያስፖራና በሀገር ቤት የሚገኙ ሁሉም የኦሮሞ ኮሚዩኒቲዎች፡ የባህልና የጥናት አካዳሚዎች፡ የወጣቶችና የሴቶች ማህበራት እንዲሁም የፖለቲካ ድርጅቶች ይህ ዘመቻ የተከፈተው በጀዋር ላይ ብቻ ሳይሆን በኦሮሞ ህዝብ ላይም እንደሆነ አጢነው ተገቢዉን እርምጃ እንዲወስዱ እናሳስባለን።

እኛም በመጀመሪያ ደረጃ ኦሮሞ ነን።

July 24, 2013
Oromo Youth Association in Europe: London/England
Oromo Women’s Association in Europe: Munich/Germany
Contact us: abasuraa@yahoo.com 

No comments:

Post a Comment