የኦፌኮ እሥረኞች፣ የብሦት አቤቱታና የረሃብ አድማ

July 20, 2013 | VOA Amharic

ቂሊንጦ የሚገኙ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ አባል የሆኑ እሥረኞች የረሃብ አድማ ላይ ናቸው፡፡

“በኢትዮጵያ እሥር ቤቶች ውስጥ በአብዛኛው ታስረው የሚገኙት የኦሮሞ ልጆች ናቸው” ያሉት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ዋና ፀሐፊ አቶ በቀለ ነጋ በቅርብ ቀን ደግሞ ከቃሊቲ እሥር ቤት ወደ አንድ መቶ የሚሆኑ እሥረኞች ቂሊንጦ ወደሚባል አቃቂ አካባቢ የሚገኝ እሥር ቤት መወሰዳቸውን አመልክተዋል፡፡

እነዚህ እሥረኞች ከሁለት ዓመታት በላይ ያለፍርድ ታስረው እየተንገላቱና ፍትሕ አጥተው እንደሚገኙ፣ ቤተሰቦቻቸው ለችግር መጋለጣቸውንና መበተናቸውን፣ እነርሱም በእሥር ቤቶቹ ውስጥ ተደጋጋሚ ድብደባ እንደሚፈፀምባቸው አቶ በቀለ ነጋ ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡

አቶ በቀለ አክለውም ሰሞኑኑ እሥረኞቹን ለመጎብኘት ወደዚያው ተጉዘው የነበሩት የአውሮፓ ፓርላማ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚቴ ልዑካን ቡድን አባላት የመንግሥት ፍቃድና ትዕዛዝ ቢይዙም በእሥር ቤቱ ኃላፊዎች እምቢተኝነት ምክንያት ሳያይዋቸው ለመመለስ መገደዳቸውን አመልክተዋል፡፡

እሥረኞቹ እየደረሰብን ነው የሚሉትን እንግልትና ያሉበትን ከባድ ሕይወት እንዲሁም ፍትሕ የዘገየባቸው መሆኑን የሚገልፅ አቤቱታቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ለፍትሕ ሚኒስትሩ፣ ለፓርላማ፣ ለሰብዓዋ መብቶች ኮሚሽን፣ ለእምባ ጠባቂ ኮሚሽን እና ለመሣሰሉት ከፍተኛ የመንግሥት አካላት ማስገባታቸውን አቶ በቀለ ጠቁመዋል፡፡

እየደረሱ ናቸው የሚሏቸው በደሎች ከቁጥጥር ዋጭ የሆኑ እንደሚመስላቸው የተናገሩት አቶ በቀለ ነጋ እሥረኞቹ አሁን የሚገኙት በረሃብ አድማ ላይ መሆኑን አመልክተዋል፡፡

ለተጨማሪ መረጃ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡

No comments:

Post a Comment