ስንብት – ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት!

March 02, 2015 | ጂቱ ለሚ

ያ ሰዉ በጣም ደስተኛ ነበር። ዛሬም ብዙዎች በየቀኑና በየቦታው 26ቱን ማይልስ በመሮጥ የዚያን ሰዉ ደስታ ያስቡታል። ሆኖም ግን ስንቶች የዚህን ታሪካዊ ክስተት ትርጓሜና አመጣጥ በዉል እንደሚገነዘቡ መገመቱ ያስቸግር ይሆናል። ያ ሰዉ ግን ስለምን እንደዚያ እንደሚሮጥ በሚገባ ያዉቀዉ ነበር። ምክንያቱም በጦርነት የታዳከመ ሰዉነቱ ሳይዝል 26ቱን ማይልስ በብቃት ሮጦ እጅግ ታላቅ የድል ዜናን ለወገኖቹ ካደረሰ በኋለ እስከ ወዲያኛዉ ኣርፈዋልና!

ዘመኑ ከክርስቶስ ልደት በፊት 490 ነዉ። ከታላቁ የፐርሽያ (Persian) ኢምፓየር ታላቅና ኃያል ሠራዊት ተንቀሳቀሰ። በግዝፈቱም፣ በታጠቀዉ መሣሪያ ዘመናዊነትና በስልጠናዉ ደረጃም የዘመኑ ዓለም ከደረሰበት ዝማኔ በላይ በእጅጉ የረቀቀ ነዉ። በዚህ ላይ ደግሞ ሽንፈትን የማያዉቅ የደረሰበትን ሁሉ ጠራርጎ የሚሄድ “የንጉሦች ንጉስ ፣ የጌቶቹ ጌታ” የተባለለት የታላቁ ንጉስ ዳሪዮስ ጦር ነዉ። እናም የቀደመ የድል ታሪኩን እያስታወሰ ታላቅነቱን እያሰበ በኩራት ተንቀሳቅሷል። ዓላማዉ ደግሞ ከወዲያ ያለዉን ሉዓላዊ መሬት በሃይል ጨፍልቆ መያዝ ነዉ። ይህ ለንጉሡ ጦር ቀላልና ተራ ነገር ነው። እናም ለዉጊያ ስልት የመረጠዉን ረባዳዉን የመራቶን ሜዳ በቅድሚያ ተቆጣጥሮ ህልሙ የሆነችው የአቴንስ ከተማ ላይ ሆነዋል።
ከወዲያኛዉ ግንባር ደግሞ በዚህ ግዙፍ ኃይል እምብዛም ግምት ያልተሰጠዉና ግዛቱን ላለማስነጠቅ ብቻ በኣራት እጥፍ የሚበልጠውን ታላቁን ጦር የተጋፈጠ የግርክ ሠራዊት ግንባር ግንባር መፋጠጥ ይዘዋል። እንዳለመታደል ሆኖ ለክፉ ቀን ተስፋ የተጣለባቸዉ የጎረቤት እስፓርታ ሰዎች እንኳ ሀይማኖታዊ በዓላቸዉን እያከበሩ ስለሆነ ሙሉ ጨረቃ በሰማይ ላይ እስከምትታይ ድረስ ወደ ጦር እንደማይገቡ ምላሽ ሰጥተዋል። እናም የቱን ያህል ከባድ ቢመስልም የአቴንስ ሰዎች ሀገራቸዉን የመከላከሉን ግዴታ ብቻቸዉን ሊሞክሩት ነዉ። ፍጥጫዉ ለዘጠኝ ቀናት ዘልቋል።
ቃታዉን የሚስብ ደፋር ከሁለቱም ወገን አልተገኘም። አንዱ የአቴንሱ የጦር አለቃ “…የሀገርህን ሉዓላዊነትና የትዉልዱን ነጻነት ኣሳልፎ ከመስጠትና እስከወዲያኛዉ ከመዋጋት የቱ ይሻልሃል?” ሲል ጠጋ ብሎ ጓዱን ጠየቀ። ጓዱም አላቅማማም። እናም ተስማሙ። ቀስት ተሳባ። ዉጊያዉ ተጀመረ።
ጠላትን ግራ በሚያጋባ የዉጊያ ስልት የሚታወቁ የታላቁ ኢምፓየር ሰዎች በፍጥነት ሰይፋቸዉን መዝዘዉ ወደፊት ተንደረደሩ። ብረት ለብረት ተጋጨ። ፉጨቱ እስከ ወዲያኛዉ የተራራ ጫፍ ኣስተጋባ። የጀግና አንገት ተቀነጠሰ። የማራቶን ሜዳ በሰዉ ሬሳ ንጣፍ ተጓዘጎዘ። የማታ-ማታ ፈጽሞ ያልተጠበቀ ክስተት ተሰማ።
የታላቁ ንጉስ ጦር፣ ያ ሽንፈትን የማያዉቅ ኃያል ሠራዊት በሰይፍ እየተመታ ሽሽት ጀመረ። የምሥራች ተነገረ – ድል ለአቴንስ ሰዎች ሆነ!
ከማራቶኑ ድል በኋላ ያ ታላቁ ኢምፓየር በሕዝቦች ዓመጽ መፈራረስ ያዘ እንጂ ፈጽሞ አልፀናም። በዕብሪት ፈረስ እንዳሻቸዉ መጋለብ የሚሹ ዝንጉዎች በቅሌት እንደሚወድቁ ዜናዉ እስከ ዓለም ዳርቻ ተናኘ። ይህንን ዘመንና ድንበር ተሻጋሪ የሆነ ቁም-ነገር ዓለም ዛሬም በቀጥታም ባይሆን በመራቶን ሩጫ ያስበዋል። እርግጥ ነዉ! ዕብሪትና ብልግና ያልተጠበቀ ዉርደትን ያስከትላል። ‘the sin of hubris’ ይሉታል ግርኮች።
ሠሞኑን በኢትዮጵያ ኢምፓየር ዙሪያ እንደተለመደዉ ዕብሪትና ብልግናን መሠረታቸዉ ያደረጉ በርካታ ግርግሮችና ዛቻዎች ተስተዉለዋል። ከሰሞነኛዉ የ”ልክ እናስገባችኋለን!” የደንቆሮዎች ድንፋታ እንጀምር።
የሕወሃት ሰዎች የዚህ ዓይነቱን ጦርነት በኦሮሞ ሕዝብ ላይ ሲያዉጁ ይህ የመጀመሪያቸዉ ባይሆንም ምናልባት ግን የመጨረሻቸዉ ሊሆን ይችላል። “ጦርነትን መስራት እንችልበታለን!” በሚለዉ በአቶ ስዬ አብረሃ ዛቻ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ የተጀመረዉ የፀረ-ኦሮሞ ጦርነት በ1992ቱ የወተሩ ጭፍጨፋ ከተረጋገጠ በኋላ፣ በአቶ መለስ ፊታዉራሪነት አድማሱን አስፍቶ ዛሬ ያልገባበት የኦሮሞ ቤት የለም ለማለት ያስደፍራል። መሬት ሲቆፈር ከየቦታዉ እንደዋዛ የሚለቀመዉ የንጹሃን ዜጎች ዓጽምና በገዛ ሀገሩ ላይ በጥይት ተረሽኖ በአደባበይ የሚሰቀለዉ ዜጋ የዚህ ዓይነቱ አዋጅ ዉጤት ስለመሆኑ አጠያያቂ አይደለም። “ፊጻሜዉ ከወዴት ያደርሰናል?” የሚለዉ ቁም-ነገር ትኩረት የሚሻ ጉዳይ ቢሆንም ይህ ዓይነቱ ግፍ የሚፈጸምበት ሕዝብ ግን መጠነ-ሰፊ አጸፋዊ እርምጃ ለመዉሰድ አይገደድም ብሎ መገመቱ ሲበዛ ተላላነት ይሆነል። የስንቱ ልብ እየደማ እንደሆነ ማን በነገራቸዉ!
በሌላ በኩል በደራና አዴት መሃከል የተቀሰቀሰው የታሪክ ሽሚያ በወያኔ/ኦህዴድ ጓዳ ዳግም ግርግር ቀስቅሷል። ስንቅና ዉሸታም እያደር ይቀላል እንደሚባለዉ የኦህዴዶች የምስረታ ታሪክ ለዓመታት ሲነገርለት ከነበረዉ ከደራ(ኦሮሚያ) ወደ አዴት(ትግራይ) በይፋ መሸኘቱ ለወገኔ ምኑም ባይሆንም በወያኔ/ኢህአዴግ ቤት ግን ገና ብዙ ያልተመዘዙ ካርዶች እንዳሉ ያመለክታል። ከዚህም ባሻገር አገልጋዮቹን ለማስደንገጥ ብሎ የሚመዛቸዉ ካርዶች ገና ከጅምሩ እየተበላሹበት ጨዋታዉን ፉርሽ እያደረጉበት መሆኑን ያስረግጣል።
እነዚህ በተከታታይ የተደመጡ የልክ ማስገባቱ ዛቻና የደራ/አዴት ጉዳይ ተደማምሮ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሆደ-ባሻነት እየታሙ በሚገኙ አንዳንድ የኦህዴድ ሰዎችና በጦሩ አባላት ዘንድ ኩርፊያ ቢጤ በመፈጠሩ “ሁሉን ዓቀፍ ዓመፅ ሊያስነሳ ይችላል’ የሚል ስጋት ቀድሞዉኑ የፖለቲካ ስሌት ለተጣረሳባቸዉ ለእነ አቦይ ፀሃዬ ዘመዶች ተጨማሪ የራስ ምታት ሆኗል።
በመሆኑም ‘የልክ እናስገባችኋለን!’ የብልግና አንደበት የሥርዓቱን መበስበስ ከማረጋገጥ ዉጪ ሌላ ዉጤት እንደማያመጣ በእርግጠኝነት ሊነገራቸዉ ይገባል። ይህ መሰሉ ትርምስና ግርግር በቀጠለበት ሁኔታ ሌላ የኢምፓየሪቷን አደገኛ አዝማሚያን የሚጠቁም ተጨማሪ ክስተት ከሌላ ጽንፍ ተስተዉሏል። የአሜሪካ ብሔራዊ የደኅንነት ምክርቤት እጅግ የነጠረ፣ ያልተዛባና በጥናት የተረጋገጠ ዘገባን ለአሜሪካ የስለላ ተቋማት፣ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አውጪዎችና ለዓለምዓቀፍ ግንኙነት ተመራማሪዎች በማቀበል ይታወቃል። ይህ ተቋም ዘመን ኣስልቶ፣ ቀን ቆጥሮና በመስረጃ አስደግፎ ኢትዮጵያ ሊጠፉ ከተቃረቡ ሀገራት አንዷ ስለመሆንዋ ግልጽ በሆነ መልኩ አቅርቦ በብዙዎቹ ዘንድ ጠንካራ ትኩረት አግኝቶ ነበር።
እናም ታዲያ የኦሮሞ ነገር ሁሌም ሕመም የሚሆንባቸዉ የኢትዮ-አቢሲኒያ ጽንፈኞች ይህንኑ እዉነታ በማጣመም ለሕመማቸዉ ማስታገሻ እንደሆነ ብለዉ ሠሞኑን ካለዉ ነባራዊ እዉነታ ጋር የሚቃረን ጭብጥ የያዘ ፊልም አሰርተዉ ሲያሰራጩ ሰንብተዋል። የፊልሙ ዋነኛ ትኩረት የኦሮሞ ሕዝብ የነጻነት ትግል ለኣካባቢዉ ቀጠና ሠላምና መረጋጋት ያለዉ ሚና ጎልቶ እንዳይታይ፤ እንዲሁም ከተቻለ በሕዝቡ ላይ እየደረሰ ያለዉን ግፍና መከራ ከዓለም ጆሮና ዓይን በማራቅ ለችግሩ ስልታዊ ከለለን መስጠት ነዉ።
ሆኖም ግን ከሀሰት ድራማና ከባዶ አንደበት የሚመነጭ የብልግና ቋንቋ ልትጠፋ ለተቃረበች ኢምፓየር ፈውስ ሊሆን አይችልምና የኢትዮ-አቢሲኒያ ጽንፈኞች ጥረት ኣልሰመረም። የደንቆሮዎች ድንፋታና የቅጠፈት ኣንደበት የሕዝቦችን ፊትሃዊ ጥያቄም ሊገታ ኣይችልም። ይልቁንም የኢምፓየሪቷን ሊበታትናት ውስጥ-ውጡን እየተንቀለቀለ ያለዉን እሳተ-ገሞራ ቢያቀጣጥል ነዉ እንጂ። እያያን ያለነዉ ሁካታም የዚሁ እዉነታ የመጨረሻ የምጥ ጣር ማሳያ ነዉ። ስለዚህም ጥንት በሌሎች ኢምፓየሮች እንደሆነ ሁሉ የጊዜ ጉዳይ እንጂ የኢትዮጵያ ኢምፓየርም በዓይናችን ፊት ትፈራርሳለች። ስንብቷም ደመቅ ያለ ይሆናል።
ይህ ሟርት አልያም ቀልድና ተረትም አይደለም። የአንባቢዎቼን ትኩረት ለመሳብ የፈጠርኩት አሉባልታም አይሆንም። ግን በእርግጥ ሊሆን ያለ ሀቅ ነዉ። እዉነት ነዉ፣ ይህ ዓይነቱን ሀቅ መስማት ለአንዳንዶች መራራ ሊሆን እንደሚችልም ኣውቃለሁ። ግን ደግሞ መሸፋፈኑ አያዋጣምና ኣይቀሬውን እውነታ ለመናገር ተገደድኩ። ከእንግዲህማ እዉነትን የማይወድ ወገኛና ነውረኛ ሁላ በቃላት ድንፋታና በሀሰተኛ ፊልም ተከልሎ ወዲያ መሻገር ይከብደዋል። ማዕበሉ በሃይል ያራግፈዋልና!
Lakkii na dhiisi siin jennaan na diddee,
Harkuma keetiin barbada haatee of gubdee!
ቸር እንሰንብት!
ጂቱ ለሚ ነኝ

No comments:

Post a Comment