ኦሕዴድ በጠቅላላ ጉባዔው ለኢሕአዴግ በሚቀርበው ሪፖርት ላይ ብቻ ተወያየ

March 07, 2013 | Ethiopian Reporter (Government's associate Press)

- ጠቅላላ ጉባዔው በሚቀጥለው ሳምንት ይሰበሰባል

የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) የካቲት 20 ቀን 2005 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔውን ለማድረግ የተሰበሰበ ቢሆንም ያልተጠበቁ አጀንዳዎች በመቅረባቸው፣ ጉባዔውን በመተው ለኢሕአዴግ በሚቀርበው የሁለት ዓመታት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ብቻ በመወያየት፣ ጉባዔውን ለሚቀጥለው ሳምንት ማስተላለፉን ምንጮች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡

የኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ጠቅላላ ጉባዔያቸውን ለማድረግ ሲሰበሰቡ፣ ድርጅቱ የተለያዩ ችግሮች ስላሉበት በአጀንዳ ተይዞ ውይይት እንዲደረግበት አንዳንድ አባላት ጥያቄ በማቅረባቸው፣ የሥራ አስፈጻሚው ኮሚቴ ሰብሳቢዎች በድጋሚ ሌላ ስብሰባ እንደሚደረግና በዚያ ስብሰባ ላይ አሉ የተባሉ ችግሮችን በማንሳት መወያየትና መፍታት እንደሚቻል ቢናገሩም፣ ስምምነት ላይ አለመደረሱን ምንጮቹ አስረድተዋል፡፡

የሕልውና ጉዳይ መሆኑን ደጋግመው በመግለጽ ራሱን የቻለ አጀንዳ ተይዞለት ውይይት እንዲደረግበት ሲጠይቁ፣ የተወሰኑ አባላት ድርጅቱ በሁለት ዓመታት ውስጥ ባከናወናቸው ሪፖርት ውስጥ የተነሳው ጥያቄ ተካቶ አንድ ላይ እንዲታይ ሐሳብ ቢያቀርቡም ስምምነት ላይ ባለመደረሱ፣ ጉባዔው እንዲተላለፍ መደረጉን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

የኢሕአዴግ ጉባዔ (ከመጋቢት 14 እስከ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.) የሚደረግበት ቀን በመድረሱ፣ በሪፖርቱ ላይ ውይይት በማድረግ ጉባዔውን ለሚቀጥለው ሳምንት እንዲሆን በመስማማት በሪፖርቱ ላይ መወያየታቸውን ጠቁመዋል፡፡

ሥራ አስፈጻሚው ለኢሕአዴግ በሚያቀርበው የሁለት ዓመታት ሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ሲወያይ በዋናነት ያነሳው ጉዳይ፣ በድርጅቱ ውስጥ የአመራር ችግር መኖሩን፣ እንደ ድርጅቱ ሳይሆን በግል የመጠቃቀም ሁኔታ እንዳለ፣ ለሥልጣን መሯሯጥ እንዳለ፣ ድርጅት ሳይመክርበት የፍርድ ቤት ሹማምንት ከኃላፊነት እንደሚነሱ፣ የግለሰቦች አምባገነንነት መንገሱን አንስተው ከተወያዩ በኋላ፣ ተገቢ አለመሆኑን መተማመናቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የፍርድ ቤት ሹማምንትን አላግባብና ሕጉን ሳይከተሉ ከኃላፊነት ማንሳት ትክክል አለመሆኑን የኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የሥራ አስፈጻሚ አባል ወይዘሮ አስቴር ማሞ ተናግረው፣ ኃላፊዎቹ ችግር እንደነበረባቸው በማስረዳት መነሳታቸው ትክክል እንደነበር መናገራቸውን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ አራቱም የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች ሕወሓት፣ ብአዴን፣ ኦሕዴድና ደኢሕዴግ በሚቀጥለው ሳምንት ጠቅላላ ጉባዔ በማድረግ የማዕከላዊ ምክር ቤት አባላትን እንደሚመርጡ ባለፈው ዕትማችን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

Ethiopian Reporter

No comments:

Post a Comment