ጁሃር መሃመድ እና የመጀመርያ ደረጃ ኢትዮጵያውያን

July 22, 2013 | Gulele Post

አመል ሚዛናዊ ዜና

በኢትዮጵያ ውስጥ እና ከኢትዮጵያ ውጭ ሁለት አይነት ኢትዮጵያውያን ይገኛሉ አንደኞቹ ቡድኖች በሚናገሩት እና በሚሰሩት ስህተት ሁሉ የሚረገሙበት የሚኮነኑበት የሆኑ ሲሆኑ ሌሎች አንደኛ ደረጃ (first degree) ኢትዮጵያውያን ደግሞ … አዬ የሳቸው ነገር አንዳንዴ እረ … ተወው…ተብለው ወደ ጎን ችላ የሚባልላቸው መርዘኛ ንግግራቸው ሁሌም (brush off) የሚደረግላቸው ቡድኖች ናቸው። የሰሞኑ የጁሃር ንግግር በየመወያያ መድረኩ እና በየፌስ ቡኩ መነጋገርያ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቷል። የጁሃር ቃላት አመራረጥ ሁላችንንም ያስከፋ ሲሆን እንኳን ከአንድ ተስፋ የተጣለበት ቀለም ጠገብ የፖለቲካ ሳይንስ ተንታኝ ምሁር ቀርቶ ከተራ ሰውም ሲሰማ አሳፋሪ እና አንገት የሚያስደፋ ነበር። ሆኖም ተመሳሳይ አሳዛኝ ንግግሮች ከሌሎች ኢትዮጵያውያን የተደመጠበት ወቅት በመኖሩ ይህ አጋጣሚ የተለየ እና አዲስ የሚያደርገው ጉዳይ በወል ባይታወቅም ሌሎች ጥርጣሬዎችን ማጫሩ አልቀረም።

ያለመታደል ሆኖ ጁሃር መሃመድ ስህተት ካልተፈቀደላቸው ቡድኖች በመሆኑ ፅንፈኛ ፣ አክራሪ እና ሌላም ሌላም (prefix and suffix) ተጨምሮለት ስሙ ረዝሞ ስመለከት አይ የኛ ነገር አድሮ ቃርያ በሚል ከዛሬ ነገ ይቀዘቅዛል ብዬ ባስብም የተባለው ጉዳይ የምናውቃቸውን የሚዲያ ባለሙያዎችንም ጭምር ስቦ በማስገባት መነጋገርያነቱ በመስፋቱ እኔም እንደ አቅሜ ለእሳቱ ማገዶ ለመጨመር ተቀላቀልኩ ።

ጁሃርን በተናገረው ሃሳብ ዙርያ ቅሬታ መኖር ብቻ ሳይሆን የተወሰኑትን ሃሳቦቹን የማልጋራቸው ናቸው። ሆኖም ይህን ወጣት ለመኮርኮም የተዘመተው ዘመቻ መስመሩን የሳተ ብሎም የተጋነነ ለመሆኑ ጥጥር የለኝም። ግን ለምን ? ኦሮሞ ይባስ ብሎ ሙስሊም የመሆኑ ጉዳይ ሳይሆን አይቀርም የሚል ጥርጣሬ አለኝ። አንዳንዱ ቆርጦ ቀጥሎ የሚያመጣው የምስል ቅንብር ህዝቦችን እርስ በርስ ላለማስማማት ቆርጦ የተነሳ ብቻ ሳይሆን ዛሬ ላይ እየታየ ያለውን የአንድነት እና የመቀራረብ በር ጥርቅም አድርጎ ለመቀርቀር የተሰናዳ ሲሆን ሌላው ደግሞ ለወያኔ ያልጠበቀውን ገፀ-በረከት ለመቀበል ታላቅ እድል ከፍቶለታል።

ከቅርብ ግዝያት ወዲህ ማለትም ባለፉት 22 ዓመታት ህውሃት ገጥሞት የማያውቀውን የፖለቲካ ኪሳራ በገጠመው በዚህ ወቅት ይህን አይነት ኪሳራ ለማወራረድ ከጁሃር የተሻለ እዳ ቀናሽ ከየት ሊገኝ ነበር? የኛ world-bank። ለዛ ነው የሰሞንኛው የጁሃር ጦርነት የተቀሰቀሰው። በጁሃር ስህተት ዙርያ የሚናፈሱት ጉዳዮች ጁሃር ከተናገረው በላይ ከጀርባቸው ለኦሮሞ ብሎም ለእስልምና ያላቸውን ጥላቻ መግለጫነት እየተጠቀሙበት ለመሆኑ ሃሜት አይደለም። ጁሃር የከፈተላቸው መንገድ በእጅጉ እንደ ምክንያት ሆኖ በውስጣቸው የተቀበረውን የእስልምና ጥላቻ መርዝ ለመርጨት ሲባል ብቻ ዛሬ ላይ የተጀመረውን የአንድነት እና የጋራ ትግል ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ለመንዳት የመስራታቸው ሚስጥር ግን ምን ይሆን?

እውነት የዚህ ወጣት ስህተት ዛሬ ሃገራችን ካለችበት አደገኛ ሁናቴ የባሰ እና የከፋ ነውን ? ወይስ ሌላ ? እንደኔ እንደኔ ዛሬም ሆነ ነገ በሃገራችን ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ካለው ህውሃት የከፋ ነገር አለ ብዬ አላምንም ይህን የጋራ ጠላት የሃገር መርገምት የሆነን ቡድን በጋራ ታግሎ ሃገራችንን ወደ ተሻለ መሰባሰብያ ቤትነት መቀየሩ ብስለት ነው ብዬ አምናለሁ። ጥላቻን ከማስፈን በላይ ቀላል ነገር የለም ሆኖም በጥላቻ እና በበቀል የተገነባ ስፍራ ግን ለሰላም እና ለለውጥ ዝንተ-ዓለም መርዝ ነው። ኦሮሞ ሆነው ከጁሃር በእጅጉ የተሻሉ አስተዋይ ምሁራኖች ፣ በሳል እና የጠለቀ የእውቀት ባለቤት የሆኑ አባቶች አሉ ፣ ስለ ሰላም ፣ ስለ መቻቻል እና ስለ አንድነት የሚሰብኩ። እነዚህ የሰላም ተምሳሌት የሆኑ የብርቅዬ ምሁራን ድምፅ ግን መሰማቱ አይፈለግም ልበል ? ስለ ህዝባቸው በደል ሆነ የመብት ገፈፋ ህይወታቸውን የከፈሉ እልፍ አላፍ ጀግኖች ኦሮሞዎች ነበሩ አሉም ይኖራሉም። እስኪህ ታድያ ማነው የነዚህን ብርዬ የስብዕና ባለቤቶች ስም አንስቶ የተሳሳቱትን ከአባቶቻቸው እንዲማሩ ምክር ሚለግስ ?

የሚያሳዝነው ክፍል ግን አላዋቂ ፀሃፍት ነን ባዮች በያገኙት ግርግዳ የሚለቀልቁት የነዚህ መርዛማ ሰዎች ቃላት ግን ለኢትዮጵያ አሳቢነታቸውን ሳይሆን የኢትዮጵያ ጠላትነታቸውን የሚያሳብቅ ነው። እስኪ በሂወት ያሉ እና የነበሩ ሌሎች ኢትዮጵያውያን የተናገሩትን ታሪካዊ እና አሳፋሪ ንግግሮች እንመልከት :-

“ አንገቱን በሜጫ እንለዋለን ” … ጁሃር መሃመድ … ኦሮሞ
“ አማራ እና ኦርቶዶክስ አከርካሪያቸውን ተመተዋል ” … አቦይ ስብሃት …ትግሬ
“ ጎንደሬ ብሎ እስላም የለም ” … የቀድሞ የመላ አማራ ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ … አማራ
“ አማራ ማለት አፍንጫ ሰልካካ ብብቱ የማይሸት ነው ” … የቀድሞ የመላ አማራ ም/ ፕሬዝደንት ደጅ-አዝማች ነቀዓጥበብ … አማራ … እንደምሳሌነት እነዚህን ጠቀስኩ እንጂ ቁጥሩ ብዙ ነው

ታድያ ምነው እነዚህ ሁሉ እኩል አልተወቀሱም አልተኮነኑም? ቢያንስ ጁሃር ገና በ20ዎች ማብቅያ እድሜ ክልል የሚገኝ ወጣት ሲሆን ከላይ ስማቸው የተዘረዘሩት ግለሰቦች ግን የድርጅት መሪዎች የነበሩ እና እድሜ ጠገብ አዛውንቶች ናቸው / ነበሩ። እንደልብ ስህተት ለመስራት የተፈቀደላቸው አንደኛ ደረጃ ኢትዮጵያውያን የፈለጉትን ሲናገሩ ሌሎች ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ኢትዮጵያውያን ደግሞ የሚሉት ሁሉ ይብጠለጠላል ልበል ? በጋራ አብሮ ስላለመኖር ሆነ ስላለመስራት በመስበክም ሆነ በማውራት ደጋፊ ማግኝ ከሱ በላይ ቀላል ጉዳይ የለም ሁሌም አዳጋቹ የሰላምን ፣ ፍቅርን ፣ መቻቻልን እና አንድነት መስብክ ብሎም ማምጣት እንጅ። ትንሹንም ትልቁንም በማራገብ ፣ በማስፋት ፣ በመለጠፍ እና ስም በማጠልሸት የሚመጣ ሰላም ሆነ ህብረት የለም በተቃራኒው ቢሆን እንጂ። የኔ አደራ የእነዚህን መርዘኛ ፅሃፍት ነን ባዮች ድምፅ በማራገብ ሆነ ድምጻቸውን አጉልቶ በማውጣት እሳት የሚያቀጣጥሉ ግለሰቦች ፣ ድህረ-ገጾች እና ሌሎች መገናኞች ከጥፋታቸው ቢታቀቡ እላለሁ።

ቸር ያሰማን

No comments:

Post a Comment