“በዝዋይ የታሰሩት ባለቤቴ እዛው እስር ቤት መሞታቸውን ሕዝብ ይወቅልኝ” – ወ/ሮ ፈሪሃ አብድርሃማን

(ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ እንደዘገበው) አቶ አህመድ ነጃሽ ሐሰን በ2002 ዓ.ም በተደረገ አገር አቀፍ ምርጫ በድሬዳዋ ክልል የኦሮሞ ኮንግረስ/ መድረክን በመወከል ተወዳድረው ነበር፡፡የፖለቲካ ተሳትፏቸውን እንዲያቋርጡ በተለያዩ መንገዶች ሲነገራቸው ቢቆዩም በሰላማዊ መንገድ ተቃውሞ ማሰማትና መደራጀት ህገ መንግስታዊ መብት መሆኑን በመጥቀስ ሲከራከሩ መቆየታቸውን ባለቤታቸው ወ/ሮ ፈሪሃ አብድርሃማን የሱፍ ለፍኖተ ነጻነት አስታውሰዋል፡፡

በ2003 የመንግስት የጸጥታ ሰዎች አቶ አህመድን በኦነግ አባልነት ተጠርጥረሃል በማለት ያስሯቸዋል፡፡የ57 አመቱ አህመድ ከታሰሩ በኋላ ለአራት ወራት ያህል በህይወት ይኖሩ ወይም ይሙቱ ለቤተሰብ ሳይታወቅ ከቆዩ በኋላ ፍርድ ቤት ቀርበው በኦነግ አባልነት ተከሰው ይፈረድባቸዋል፡፡ፍርዳቸውን ተከትሎም ለምርመራ ከቆዩበት ማዕከላዊ ወደ ዝዋይ ወህኒ ቤት እንዲዘዋወሩ ይደረጋሉ፡፡
ከአቶ አህመድ ነጃሽ ያገኟትን አንድ ልጅ ለብቻቸው የማሰደግ ዱብ ዕዳ የወደቀባቸው ወይዘሮ ፈሪሃ ገቢያቸው በመቋረጡ ስራ ፍለጋ ወደ አረብ አገር ያቀናሉ፡፡በአረብ አገር ያለሙትን ማግኘት ባለመቻላቸው ወደ አገር ቤት ይመለሳሉ፡፡ካልተሳካው ስራ ፍለጋ መልስ ወይዘሮዋ ባለቤታቸውን ለመጠየቅ ወደ ዝዋይ ሲያመሩ የማረሚያ ቤቱ ሃላፊዎች ባለቤታቸው ወደ ቃሊቲ መዘዋወራቸውን ይነግሯቸዋል፡፡
ከዝዋይ በቀጥታ ወደ ቃሊቲ በማምራትም ይጠይቃሉ፣ቃሊቲዎች እንዲህ አይነት እስረኛ ወደ እነርሱ አለመምጣቱን በመጥቀስ ያሰናብቷቸዋል፡፡ከብዙ የዝዋይና ቃሊቲ ምልልስ በኋላ አቶ አህመድ በጠና ታመው ምኒሊክ ሆስፒታል እንደገቡ ይነገራቸዋል፡፡ምኒልክ ሆስፒታል ለጥየቃ ባመሩበት ወቅት መጥፎውን ዜና ይሰማሉ፡፡አቶ አህመዲን ይህችን አለም ከተሰናበቱ ረዘም ያሉ ወራቶች ተቆጥረዋል የሚል፡፡
አስከሬን የለ፣ የት እንደተቀበሩና የሞታቸው መንስኤ ምን እንደነበር የሚያስረዳ የለ፣ ሁሉ ነገር ድፍንፍን ያለባቸው ወይዘሮዋ ለፍኖተ ነጻነት በሰጡት ቃል‹‹የመንግስት ሰዎች ምንም አይነት ቀና ምላሽ እንደማይሰጡኝ አውቃለሁ ነገር ግን በታሰሩበት ወቅት ፍጹም ጤነኛ የነበሩት ባለቤቴ መሞታቸውን ህዝቡ ይወቅልኝ ብለዋል፡ ፡የኦሮሞ ኮንግረስ በኋላም የኦፌኮ ፕሬዘዳንት የሆኑት ፕሮፌሰር መራራ ጉዲና የአቶ አህመድን ሞት ከባለቤታቸው እንደሰሙ በመጥቀስ ነገር ግን ምንም ማድረግ አለመቻሉን አውስተዋል፡፡

No comments:

Post a Comment