ኢሳት (ESAT) – ትልቁ ዳቦ ሊጥ ሆነ! ኢሳት አደገኛ አካሄዱን ካላቆመ መዘዙ ብዙ ነው

February 24, 2014 | By Dambal Galaala

በዚህ ሰሞን (February 17, 2016) እፍታ የኢሳት ቴሌቭዢን ፕሮግራም አይቼ ነበር:: https://www.youtube.com/watch?v=KZc3yLHerqM ሲሳይ አጌና እና ካሳሁን ይልማ በኦሮሚያ ውስጥ እየተካሄደ ስላለው ህዝባዊ ትግል በተለይም በሻሸመኔ ዙሪያ ስላለው ሁኔታ ያደረጉት ወይይት የሚገርም ብቻ ሳይሆን የሚይስተዛዝብም ጭምር ነው:: ያለማጋነን በኢትዮጲያን ቴሌቭዢን መስኮት እነ አቶ ጌታቸው ረዳን ያየሁ ነው የመሠለኝ::
            

አቶ ሲሳይ አጌና እና ካሳሁን አቶ ይልማ ኦሮሚያን በተመለከተ ባደረጉት ውይይት ትኩረት የሰጡት በአክራሪነት ላይ ነው:: ይህ “ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ” የሚባለው ነው:: የኦሮሞ ህዝባዊ ንቅናቄንና አክራሪነትን ምን ያገናኘዋል? የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ፍትሓዊና ህገ-መንግሥታዊ መሆኑን ዓለም ያወቀው መንግሥስት ራሱ ያመነውና እነሱም (ኢሳቶች) ራሳቸው ሲዘግቡበት የነበረ ነው:: ከዚህ በፊት በሌሎች ብሔር ተወላጆችና በእምነት ተቋማት ጥቃት ሲደርስ “በመንግሥት የተቀነባበረ ሴራ ነው መረጃም አለን” ሲሉን አልነበረም? ታድያ አሁን ከሰርግ ሲመለሱ የነ ሀጫሉ ሁንዴሳን ዘፈን በማደመጣቸው የተገደሉት ሰማዕታት ውስጥ አክራሪነትን መፈለግ ምን አመጣው?
ይህ በተለይ ከሳምንታት በፊት ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ዋሽንግተን ዲሲ ላይ ባደረጉት ንግግር የኦሮሞን ህዝባዊ ንቅናቄ በተመለከተ ከተናገሩ በሗላ የመጣ የአቋም ለውጥ ነው:: ዶ/ር ብርሃኑ በንግግራቸው ውስጥ በብሔር ላይ የተመሠረተ የፖለቲካ አደረጃጀትን እንደሚቃወሙና በአሁኑ የኦሮሞ ህዝባዊ ንቅናቄ ውስጥም አክራሪ ኦሮሞዎች እንዳሉ ጠቁመው ነበር:: ዶ/ር በርሃኑ ይህንያሉበት ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉ:: አንደኛው ምክንያት ዶ/ር ብርሃኑና ፓርቲያቸው የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ለእነሱ የፖለቲካ ዓላማ እንደማይምችና ምናልባትም እንቅፈት እንደሆነ ያምናሉ:: ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የኦሮሞ ህዝብ ንቅናቄን ለራሳቸው የፖለቲካ ግብ ለመጠቀም የነበራቸው ህልም ያለመሳካት ነው::
እንደሚታወቀው የነ ዶ/ር ብርሃኑና ፓርቲያቸው የኦሮሞ ህዝብ ንቅናቄን ለራሳቸው የፖለቲካ ግብ ለመጠቀም የነበራቸው ህልም ያልተሳካው በሁለት ምክንያት ነው:: አንዳኛው እነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ በተለይ የአማረው ህዝብ የኦሮሞን ህዝብ ትግል እንዲደግፍና እንዲቀላቀል ጥሪ አቅርበው ነበር:: ይህ ጥሪያቸው ያልተሳካላቸው ደግሞ ህዝቡን ማደራጀት በለመቻላቸው ነው:: ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የኦሮሞ ህዝብን ጥያቄ እንደፍለጉት ጥምዝዘው ለፈለጉት ዓላማ መጠቀም ባለመቻላቸው ነው:: እንደሚታወቀው የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ከመጀመርያ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ የማንነት የፖለቲካ ነፃነት እና የሀብት ባለቤትነት ህገ-መንግሥታዊ ጥያቄ ሆነው ቀጥሏል:: ይህ ደግሞ ለነ ዶ/ር ብርሃኑ ቡድን ራስ ምታት ሆኖባቸው ሰንብተዋል::
የግንቦት 7 መሪዎችና ኢሳቶች ደግሞ ለህመማቸው ማስታገሻ ብለው ያሰቡት ደግሞ በተቻላቸው መጠን የኦሮሞን ህዝብ ትግል ማዳከም ነው:: በእነሱ አስተሳሰብ ይህ የሚሳካው ደግሞ ኦሮሞው እርስ በራሱ እንዲጠራጠር እና ከለሎችም መህበርሰቦች ጋር በጥርጣሬ እንዲተያይ በማድረግ ነው:: ለዚህ የመረጡት አሻጥር በኦሮሞ ሰልፈኞች ውስጥ አክራሪዎች እንዳሉና ተቃጥሏል የተባሉ ቤተእምነቶችንም ያቃጠሉት እነዚሁ ሰልፈኞች እንደሆኑ ማስመሰል ነው:: ዛሬ በኢሳት እፍታ ፕሮግራም ላይ ያየነውም ይሄው ነው:: በመንግሥት ደጋፊነት የሚታወቀው ሪፖርተር ጋዜጣ እንኳን በተስካን ተቃጥሏል በተባለበት አካባቢ መስጊዶችም መቃጠላቸውን ሲዘግብ ኢሳቶች ለምን በተስካኖች ላይ ብቻ ለማትኮር እንደፈለጉ ግልፅ አይደለም::
ዛሬ ኢሳት የሰራውም ሥራ መንግሥት ከሚሠራው ሥራ ይመሳሳላል:: ግን ደግሞ በጣም ያስተዛዝባል:: የግንቦት 7 መሪዎች ኢሳቶችም ሆኑ ማንም መሳሳት የሌለበት አንድ ነገር ግን አለ:: ክርስትናም እስልምናም ዋቄፈናም የኦሮሞ እምነቶች ናቸው:: በተስካኖችም ሆኑ መስጂዶች የኦሮሞ ቅርስና ንብረቶች ናቸው:: የኦሮሞ ህዝብ እምነቶቹንና ንብረቶቹን ከማንም ፍቃድ ሳያስፈልገው መንከባከብና መጠበቅ ይችላል ይህንንም እያደደረገ ይገኛል::ዋናው ነገር የኦሮሞ ህዝብ ትግሉን አጠናክረው ይቀጥላል:: ኢሳትም ከህዝብ በሚሰብስበው ገንዘብ ከሚያደርገው እኩይ ተግባሩ ቢቆጠብ ይሻለዋል::

No comments:

Post a Comment